Tuesday, September 7, 2021

በእንተ ሃዲስ ዕዝራ

ወርሃ ጳጉሜን ወርሃ ምስጢር   ዕለተ ሠሉስ ጳጉሜን 02 2013 ዓ.ም

 ከእርሳቸዉ ጋር ስሆን ከደስታዬ ብዘት የተነሳ ሲናገሩ ሳቅ ሳቅ ይለኛል፤

አርጅቶ እንኳን በአልጋ አድርገዉ እያመጡ ያስተረጉሙት የነበረዉን ባስልዮስ ዘ ቂሳርያን ያገኘሁት ይመስለኛል፤

ሁሉ ነገራቸዉ ይገርመኛል፤

አንዴ ግን በጣም ሳልቀርባቸዉ ሳንተዋወቅ ምሽት 1፡00 አካበቢ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ጎንደር ጉባኤ ጨርሰዉ ሲዎጡ ወደ ጉባኤ ቤቱ ጠጋ አልኩና ሰላምታ ሰጠኋቸዉ፤ ከዚያ ሁሌም የማይመለስልኝ ጥያቄ ነበር የቅዱስ ሚካኤል እና የቅዱስ ገብርኤል ጉዳይ፤

ሠለስቱ ደቂቅን የሁለቱም ድርሳን ላይ ሁለቱም እንዳዳኑ ተጠቅሷል፤ እርስዎ  ምን ይላሉ አልኳቸዉ፤

የኔታ ሊቁ ዕዝራ ትንሽ አሰቡና እንደተለመደዉ ወደ ሰማይ ቀና ብለዉ አዩ፤ ክስት ሊተ እንደ ማለት ፤

እኔ ጓጉቼ ዓይን ዓይናቸዉን አያለሁ፤ አጭር ቃል ተናገሩ ፤

ቅዱስ ሚካኤል ካለበት ቅዱስ ገብርኤል አይታጣም ፤ አንድ ክንፋቸዉ የገጠመ ነዉ አንድ ክንፍ ለሁለት ነዉ የሚጠቀሙት ሲሉኝ እጅግ ስለፈራሁ ሌላ ጥየቄየን ሳላስከትል “ ፍልጥ ዘትትዋነይ ኦ ገብረ ማርያም ንዑስ ” አንተ ትንሽ ሰዉ አቅምኽን እወቅ ብዬ ሹልክ ወደ ቤቴ……… ከዚያ በኋላ ምስጢር መርማሪ ሆንኩ እላችኋለሁ፤ እነ ጥራዝ ነጠቅ ያሳዝኑኛል፤

ብጹአዊ አባታችን አቡነ ኤልሳ በሕይወተ ስጋ ሳሉ የኔታ ሊቁ ዕዝራ ሲያስተምሩ እጅግ ስለተደሰቱ የረቀቀ ስም ሰጧቸዉ ዕዝራ ሃዲስ የሚለዉን የራሳቸዉን ስም በመገልበጥ ፤ ሃዲስ ዕዝራ አሏቸዉ አንተ ሁሌም አዲስ ነህ ለማለት ………..

ከእርሳቸዉ ጋር ለ8 ዓመታት በጉባኤ ቤቱ አስተባባሪ ኮሚቴነት የሒሳብ ሹም ሁኜ ተገልግያለሁ፤ የስጋ ነገር ሁኖ ቢሮ እየዋልን እንጂ 8 ዓመት ጉባዔ ባሔድ ኑሮ መጋቤ ብሉይ ወሃዲስ ወሊቃዉንት የሚል ስም ይለጠፍልኝ ነበር ፤ ዋናዉ ግን መብረቅ ይወልድ መብረቀ እንዲል እርሳቸዉን አስመስለዉ እንጂ እርሳቸዉን አሳክለዉ የወለዷቸዉ የሉም ፤ ግን እንጠብቃለን !

እንዲህ ዓይነት ሰዎች ሲያልፉ ነዉ የሚወደሱት፤ ሲቀሩብን ነዉ የምናዉቃቸዉ፤ እጅግ ብዙ ዉስጣዊ ፈተናዎችን አስተናግደዋል፤ ተሃድሶ መናፍቃን ከእግራቸዉ ስር ይፈላሉ፤ የቅርብ ሰዎቻቸዉ በተለያየ ሁኔታ ይዘምቱባቸዋል ነገር ግን እርሳቸዉ ሁሌም አንድ ነገር ይናገራሉ ……. የጉባዔዉ አምላክ እርሱ ባለቤቱ ያዉቃል ይላሉ፤

የንግሥ በዓላት ድምቀት ናቸዉ ፤ ሊቃዉንት ከእርሳቸዉ ፊት ሲሆኑ ምስጢርን ማራቀቅ ማንነታቸዉን ለማሳየት ይሽቀዳደማሉ፤ የመንግሥት ባለስልጣናት ታሪክ አዋቂ በመሆናቸዉ ይፈሯቸዋል፤ የጵጵስና ማዕረግ ቀርቦላቸዉ አሻፈረኝ ብለዋል ላለመቀበል ሳይሆን ብዙ ለመስራት ሲሉ፡፡

በትምህርታቸዉ በመድረካቸዉ በጉባዔያቸዉ ኢንጂነር፣ የባንክ ባለሞያ ፣ ፔዳጎጂካል ፣ የኢኮኖሚ ተንታኝ፣ ፖለቲከኛ፣ አስታራቂ ፣ የጤና ባለሞያ፣ ፈላስፋ ፣ ቲያትረኛ፣ ሃያሲ፣ ጋዜጠኛ፣ ዲፕሎማት ፣ ጠበቃ ፣ ዳኛ ፣ወታደር፣ ሁነዉ ታገኟቸዋላችሁ፤

ጥበቡን መድኃኔዓለም በግልጽ እንደሰጣቸዉ ያስታዉቃል፤ ነገር ግን እርሳቸዉ ጋሻጃግሬ አስተዋዋቂ ስለሌላቸዉ ከእነ ኣያ እገሌ እኩል አይታወቁም፤ በቤተክርስቲያኗ ቴሌቪዥን እንኳን ከብዙ ጊዜ በኋላ ነዉ ብቅ ያደረጉዋቸዉ የሚያዳርሱትን ካዳረሱ በኋላ፤ አበዛሁ መሰለኝ

አንድ ብቻ ነገር ልንገራችሁ እና ላብቃ ፡

ከእኔ ጋር ለጉባዔ መተማ ዮሐንስ ከተማ ጥር 04 ቀን 2008 ዓ.ም እየወሰድኳቸዉ የነገሩኝን ላካፋላችሁ እጅግ በጣም ስለገረመኝ፤

ደብረ ሊባኖስ ለትሩፋት ከጻድቁ በረከት ለማግኜት ሄድኩና አልባሌ ልብስ ለብሼ የሹራብ ቆብ አድርጌ ለሁለት ሳምንታት ለተጠማቂዉ ጸበል ስቀዳ ሰነበትኩ ፤ በኋላ አንዲት ሴት አወቀችኝ በምን አወቅሽኝ ስላት ሳቅ ስትል በጥርስህ አወቅኹኽ አለችኝ በኋላ መነኮሳት ተሰብስበዉ አስተምረን ብለዉኝ አስተምሬ ብዙም ሳልቆይ ወደ ጎንደር ተመለስኩ፤ እና ሰዉ ልታወቅ እወቁኝ ካለ በቀላሉ ይታወቃል እራሱን ልደብቅ ካለም እንደዚያዉ ፤ ያሉኝ ሁሌም አይረሳኝም ፤ መተማ የሆነዉን ብዙ ድንቅ ነገር አላነሳም ግን በትምህርታቸዉ ሙስሊሞች ተጠምቀዋል፡፡

በለተይ ጎንደርን የሃይማኖት ተጠያቂ በመሆኗ ፈጣሪ ያለ አንድ ሊቅ እንደማይተዋት ማረጋገጫችን ስለሆኑ መድኃኔዓለም ከክፉ ሁሉ ይጠብቅልን፤ እኔም ትንሽም ቢሆን ከእርሳቸዉ ጋር በነበረኝ ቆይታ ምስጢርን እንዳዉቅ እንድመረምር እና በዕምነቴ በሃይማኖቴ በራስ መተማመን እንዲኖረኝ ያደረገኝ ፈጣሪ ክብር ምስጋና ይድረሰዉ፤ አሜን + + +

Wednesday, August 25, 2021

ማርያም ማለት ገነት መርታ የምታገባ ማለት ነዉ

     
  ፍልሰታ ለማርያም !

 ሕጻናት በፍቅር የሚጾሟት እነ ቀዉስጦስ መልአክ እና አባ ሳሙኤል ዘደብረ ቀልሞን በምስራቅ በኩል ለሚቆሙ ለሚያስቀድሱ በቤተልሔም አካባቢ በረድኤት የሚገለጹበት ሱባዔ፤ እመቤታችን ድንግል ማርያም ከቅዱስ ሚካኤል እና ከቅዱስ ገብርኤል ጋር በይበልጥ ኢትዮጵያን እና ሕዝቦቿን ተገልጣ የምትባርክበት ሳምንታት፤

አንቲ ዉእቱ ማዕጠንት ዘወርቅ እንተ ጾርኪ ፍሕመ እሳት ቡሩክ ቡሩክ እሳት የተባለ ልጇ እንዴት ያለ እሳት ነዉ ቡሩክ የሆነ እሳት እያልን የቅዳሴ ተሰጥኦ የምንቀበልበት የሚናፈቅ ጊዜ፤

መክፈልት ዳቦ እንጀራ ቋጥረን ደጄሰላሙ ላይ አስቀምጠን ሠራዊተ መላእክቲሁ ለመድኃኔዓለም ሲባል ቁርባናችን እንደደረሰ አዉቀን በየጾታችን ተሰልፈን ቆርበን ወደ አስቀመጣናት ምግብ ስንሮጥ አንዳንዴ እርስ በእርስ መሰራረቁም ነበር፤

ታዲያ መላእክት አብረዉን አስቀድሰዉ ሕጻናት በመሆናችን ቂም በቀል ስለሌለን ከእኛ ጋር መቆየታቸዉ ደስ ቢያሰኛቸዉም ቅዳሴዉ ሲጠናቀቅ ጸሎቱን፤ ቁመቱን መስዋዕቱን ማሳረግ ስላለባቸዉ ከሁለት ሰዓታት በኋላ ይለዩናል፤

አሁንማ ታላላቆች ሁነናል ቆመን ማስቀደስ ብንችልም ቂም ይዘን ተጣልተናል ንስሐ ሳንገባ ጾሙ ገብቷል፤ እስከማታ ብንጾምም እንደ ሕጻናት ስላልሆንን መላእክት ርቀዉናል፤

ቂም ይዘን ተጣልተን ሰዉ አስቀይመን፤ ሰርቀን፤ ባዕድ አምልከን ዘሙተን፤ ሁለቱን ሱባዔ (ሳምንት) ጥሬ እየቆረጠምን ከምንጾም እንደ ሕጻናት ሁነን አንድ ቀን ብንጾም ሳይሻል አይቀርም፡፡

ለግብጻዉያን በግንቦት ወር በደብረ ምጥማቅ እንደምትገለጸዉ ነሐሴ ወር በተለይ ለኢትዮጵያዉያን ነጭ ሰበኗን ለብሳ ቅዱስ ሚካኤል በቀኝ ቅዱስ ገብርኤል በግራ ሁነዉ የምትገለጽበት መሆኑ የታወቀ የተረዳ ነዉ፤

በዓለም ባሉ በኦርቶዶክሳዉያን አብያተ ክርስቲያናት የሚቆመዉ ቁመት የሚታጠነዉ ማዕጠንት፤ የሚሰዋዉ መስዋእት የሚያርገዉ በአክሱም ጽዮን (ለዓለም በተሰጠችዉ በሙሴ ጽላት) አማካኝነት ነዉ ብንልም ማንም አይሰማንም፤ ኢትዮጵያ የምስጢር ሃገር ናትና ሰላም እንዳታገኝ ከንቱዉ ዲያብሎስ ከፈጣሪ አየቀረበ እባክህ ተወኝ ልፈትናት ይላል፤ ንግስናዉን በመሳሪያ እና በወታደር ካስቀየረ እና ንጉሱን ካስገደለ ጳጳሱን ካሰቀለ በኋላ ደም እያስፈሰሰ እሱን እየላሰ ይኖራል፤

ሱባዔዉን ኃይለ መስቴማን የሚያደክም ሱባዔ ያድርግልን ክፉ ትዉልድ ባያምንበትም አስራት ትሁንሽ የተባለችዉን ሃገራችንን እመቤታችን በጸሎቷ ለሷ ባለን ፍቅር እና ክብር ተመልክታ ዲያብሎስን ታሳፍርልን፤ በደመ ነፍስ የሚገዳደሉትን ቤተሰቦች ታስታርቅልን፤ ያለ ጽዮን እርቅ የለም፤ እድሉ ከተገኜ በጽዮን በደጇ በአበዉ ደናግል መነኮሳት እና ቀሳዉስት ሁለቱም አሽከሮች ይታረቃሉ፤ እምቢ ካሉ ሠይፍ ይበላቸዋል፤ ስዉሩ ነአኩቶ ለአብ ይገለጣል፤ ብረት አንጋቢዎችን ብረቱ ላይ ያሉትን መስተቃትላን አጋንንትን አስወግዶ አስተዋይ ልቦና ይመጽዉትልን፤ አሜን + + +